እንዲህ ሆኜ አውቃለሁ …
ሳልበላ ሳልጠጣ ሳልታጠብ ሳልተኛ ውዬ አድሬ አውቃለሁ፤
የለበስኩትን ሳልቀይር ጫማዬንም ሳላወልቅ ተኝቼ ፤
እንደዛው ተነስቼ ጠዋት ወጥቼም አውቃለሁ
ቀን ከሌሊት አልቅሻለሁ
ጨልሞብኝ ራሴን ጠልቼ
ለእንቅልፍ ኪኒን ውጬ አሸልቤአለሁ
ከአቅም በታች ኖሬ አውቃለሁ
ያልተፈለግኩ የምድር ጥራጊ ፤
የእንግዴ ልጅ ውዳቂ የሆንኩ መስሎኝ ያውቃል ፤
ከለሊቱ 8 ሰአት ከቤት ወጥቼ እስኪነጋ ከተማውን ሳካልል ስዞር አድሬ አውቃለሁ ፤
ለሰአታት ዝናብ ላይ ተቀምጬ አውቃለሁ፤
እንቅልፍ አጥቼ አውቃለሁ
ቀን እና ሌሊት ተኝቼም አውቃለሁ
ረዥሙን ፎቅ ሽቅብ በዓይኔ ለክቻለሁ
የገመዱን ጥንካሬ በእጄ ገምቻለሁ
የመርዙን ንጥረ ነገር google አድርጌ ፈትሻለሁ
ብዙ ብዙ ሆኜ አውቃለሁ ፤
ድጋፍ አጥቼ ሟሙቼ ፤ ቆዳዬ ጠቦኝ ሳስቼ
ነፍሴን ማሰንበቻ ምክንያት አጥቼ አውቃለሁ
ማውራት፣ መስማት፣ መስራት፣ ማሰብ፣ መፃፍ፣ ማንበብ መኖር በጠቅላላ ደክሞኝ ያውቃል
ሰማይ ተከድኖብኝ ምድር ተንሸራታ ከድታኝ ፤
ከነልብስና ጫማዬ ሻወር ገብቼ ውሃ በላዬ ለቅቄ ለሰዓታት ተዘፍዝፌ አውቃለሁ፤
አንዳንድ ቀን ያሳክከኛ፤ አንዳንድ ቀን ይሞቀኛል ልብሴን እጥላለሁ፤ ሌላ ቀን ይበርደኛል እንዘፈዘፋለሁ
ታምሜአለሁ አንዳንድ ቀን ወደላይ፤ አንዳንድ ቀን ወደታች ይለኛል ፤ አንዳንድ ቀን ነስር፤ አንዳንድ ቀን እንባ፤
አንዳንድ ቀን ቁርጠት፤ አንዳንድ ቀን ራስ ምታት፤
አንዳንድ ቀን ማቅለሽለሽ፤ ሌላ ጊዜ ማንቀላፋት፤
ከሁሉ የባሰው ማመን ያቃተኝ ነገር ራሴን ካስቀመጥኩበት ሳጣት
ራሴን እዚህ ቦታ ሳገኛት
ያቺ ሰው ሁሉ “ጎሽ ጎሽ” የሚለኝ ፤የሚወደኝ፤ ድክመት የማይገኝብኝ ፤ ጥንቅቅ ስትር ያልኩ
የሚያውቀኝ ሁሉ የሚያጨበጭብልኝ
“ጠይም ጽጌረዳ”ኮ ነኝ
እንዴት ሆኖ ምን ሲደረግ? ድካሜ የማይታይ፤
‘እንደሷ ሁኑ’ የሚባልልኝ ነኝኮ …
ግን ሆኜ አውቃለሁ
ከመቼ ጀምሮ እንደዚህ አይነት ሰው ሆንኩ እልና እልህ ያፍነኛል ደግሞ
የሆንኩትን መቀበል ያቅተኛል
ያቺ መካሪዋ ሰው አጽናኟ ብርቱ የማትደክመዋ
እኮ እኔ?
አሁን የት ነኝ? ያቺት እዛ ጥግ ስርቻ ስር ተወትፌ ሸረሪት የሚያደራብኝ
እንኳን ለሰው ልደርስ ድረሱለኝ ማለት ያቃተኝ
ከራሴ መሸሺያ ያጣሁ ሁለንተናዬን ጠልቼ ከራሴ ሮጪ የማላመልጥ ምስኪን
የማውቀውን እንደማላውቅ ያለኝ ሁሉ እንደሌለኝ ሆኜ ሁሉን ከዜሮ ጀምሬ አውቃለሁ
ድካምና ጉስቁልና ተጭኖኝ የማለቅስበት ፈልጌ አጥቼ ጉልበቴን አቅፌ ቀርቼ አውቃለሁ
ብቻ ብዙ ብዙ ብዙ ነገር ሆኜ አውቃለሁ ፤
አልፎ እንደዚህ ላወራው ልፅፈው ከቻልኩ
ድምጽ አውጥቼ ይሄንን ካልኩ ፤ እናንተም ከሰማችሁ
ዛሬም ከነጋ ‘ግድ የለም ተስፋ አለኝ’ እላለሁ
እንግዲያውስ ተስፋ አለኝ !
ተስፋ አለኝ እላለሁ
ተስፋ አለኝ እላለሁ
ተስፋ አለኝ እላለሁ
ተስፋ አለኝ!
